“የዓባይ ግድብ እና ዓድዋ የአንድነታችን ማሰሪያ የቁጭታችንም ማሳያ ስኬቶቻችን ናቸው” – ዶ/ር ኢ/ር ሀብታሙ ኢተፋ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር

“የዓባይ ግድብ እና ዓድዋ የአንድነታችን ማሰሪያ የቁጭታችንም ማሳያ ስኬቶቻችን ናቸው” – ዶ/ር ኢ/ር ሀብታሙ ኢተፋ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዓባይ ግድብ እና ዓድዋ ድል የአንድነታችን ማሰሪያ፤ የቁጭታችንም ማሳያ ስኬቶቻችን ናቸው ሲሉ የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ:: ሁለቱም ስኬቶች በሕዝቡ እና በመሪዎች ቅብብሎሽ የተገኙ ድሎች መሆናቸውን አስታወቁ:: የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ (ዶ/ር) ከአዲስ ዘመን ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳስታወቁት፤ የዓባይ ግድብም ሆነ ዓድዋ የኢትዮጵያውያን አንድነት የተረጋገጠባቸው ስኬቶች ናቸው:: ኢትዮጵያውያውን በሁለቱም ላይ አንድነታቸውን አሳይተዋል፤ በቁጭት በሠሩት ሥራ የማይደፈር ማንነት እንዳላቸው አረጋግጠዋል:: ሁለቱም ታላላቅ ስኬቶች ኢትዮጵያውያን በብቃት የተጫወትንባቸው ሜዳዎች ናቸው ያሉት ሚኒስትሩ፤ ጠላትን በዝረራ ከጨዋታ ወጪ ያደረግንበትን ድልም አስመዝግበንበታል ብለዋል:: ዓባይ ግድብ ሆነ ዓድዋ ድል ኢትዮጵያ ይደርስባት የነበረውን የውጭውን ጫና በብቃት የመከተችበት ሲሆን፤ ያንን የተሳሳተ አስተሳሰብ ያኮላሸችበት ስኬቷ እንደሆኑም ገልጸዋል:: እንደ ኢንጂነር ሀብታሙ (ዶ/ር) ገለጻ፤ ዓድዋ ድል እና ዓባይ ግድብ የኢትዮጵያውያን አንድነት የተረጋገጠባቸው ናቸው:: ዓድዋ ላይ እንደ አሁኑ ጊዜ ቴክኖሎጂ አልነበረም:: ተንቀሳቃሽ ስልኩ፣ ኢንተርኔቱ እና ሌላ ሌላው አልነበረም:: እንዲያም ሆኖ ለኢትዮጵያ አንድነት ሲባል ከጥግ ጥግ ድረስ በአራቱም ማዕዘን ንቅናቄ በመፍጠር ኢትዮጵያ የእኔ ናት ብሎ ስለሚያምን ለኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ሕዝቡ መንቀሳቀስ ችሏል:: በወቅቱ የራሱ የሆነና እንዲፈታለት የሚፈለገው ችግር ሊኖርበት ይችል ይሆናል:: ነገር ግን በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ድርድር አያውቁም:: የዓባይ ግድብም በተመሳሳይ የሚጠቀስ ነው:: የዓባይ ግድብ በየትኛውም ክልል ሆኖ የትኛውም ቀበሌ ውስጥ ያለ ሰው ዓባይ ሲባል አንዳች የአንድነት እና የመተባበር መንፈስ ውስጡ እንዳለ ይታወቀዋል:: የእኔነት ስሜቱ የጎላ ነው:: ምክንያቱም ከሌለው ነገር ላይ ለዓባይ ግድብ አቋድሷል:: በዓድዋ በኩል ወይ ራሱ አሊያም ልጆቹን ወደ ግንባር እንዳላከ ሁሉ ለዓባይ ግድብም እንዲሁ በጉልበቱ፣ በገንዘቡና በሀብቱ ተሳትፏል:: ከዚህ መነሻነትም ዓድዋ ድልና ዓባይ ግድብ የአንድነት ማሳያ ናቸው:: ሁለቱም የኢትዮጵያውያን ምልክት ናቸው:: ሚኒስትሩ፣ ሁለቱም የውጭ ጫና የፈተናቸው ታላላቅ ስኬቶች ናቸው:: ኢትዮጵያ በዓድዋ ጦርነት ጊዜ የተዋጋችው አንድን ሀገር ብቻ አይደለም:: በወቅቱ ከጣሊያን ጋር ኅብረት ከፈጠሩትና የቅኝ ግዛትን ማስፋፋት ከሚፈልጉት ሀገራት ጋር ሁሉ ነበር ማለት ይቻላል:: ኢትዮጵያ በወቅቱ ያሸነፈችው የተነሱባትን ኃይሎች ሁሉ ነው:: ይህ ትልቅ ስኬት ነው ብለዋል:: የዓባይ ግድብን በተመለከተ ደግሞ እኛን ስትገዳደረን የነበረችው ግብጽ ብቻ አይደለችም ያሉት ኢንጂነር ሀብታሙ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ ማሸነፍ የቻለችው በድህነቷ እንድትዘልቅ የሚፈልጉ ኃይሎችን ጭምር እንደሆነ አስረድተዋል:: ኢትዮጵያ በዓባይ ግድብ ምክንያት በጸጥታው ምክር ቤት ስትወሰድ ዓላማው ኢትዮጵያን በዚያ ደረጃ ማብጠልጠል ነው:: በመሆኑም በኢትዮጵያ ጥንካሬ እሱን ወደ አፍሪካ ኅብረት መመለስ መቻል ትልቅ ስኬት ተደርጎ የሚወሰድ መሆኑን አመልክተዋል:: በዓድዋ ጊዜ በውጊያ የነበረው የቅኝ መግዛት ሕልም ኢትዮጵያ እንዳጨናገፈች ሁሉ አሁን ደግሞ በኢኮኖሚው በኩል በቅኝ ለመግዛት የተቋመጠውን አካሔድ ኢትዮጵያ ያሸመደመደችው መሆኑ ሁለቱን የሚያመሳስላቸው ጉዳይ ነው ብለዋል:: እርሳቸው እንዳሉት፤ በጣም ወሳኙ ጉዳይ በኢትዮጵያ የውሃ ልማት ታሪክ ዛሬ ያመጣነው ስኬት በአንድ ጀምበር የመጣ ሳይሆን በትውልድ ቅብብሎሽ የተገኘ ስኬት ነው:: በዚህ ስኬት ውስጥ የመሪዎች ቅብብሎሽ አለ:: ንጉሱ አጼ ኃይለስላሴ የአሜሪካ ኩባንያ ቀጥረው ኢትዮጵያ ውስጥ ለግድብ የሚሆን ብዙ ቦታ ካስጠኑ በኋላ ብድር ጠይቀው ተከልክለዋል:: ይሁንና አንድ ቀን ኢትዮጵያውያኑ እንደሚገነቡት ተስፋ አድርገው አልፈዋል::

Share this Post