የኦሞ -ጊቤ የተፋሰስ ዕቅድ ቴክኒካል ኦዲት ሪፓርት የባለድርሻ አካላት መድረክ እየተካሄደ ነው።

የኦሞ -ጊቤ የተፋሰስ ዕቅድ ቴክኒካል ኦዲት ሪፓርት የባለድርሻ አካላት መድረክ እየተካሄደ ነው።

ጅማ # ግንቦት 07/2018 ዓ.ም.በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በሚተገበረው የብራይት (BRIGHT) ፕሮጀክት አማካኝነት የተዘጋጀው የኦሞ-ጊቤ ተፋሰስ ዕቅድ ቴክኒካል ኦዲት ሪፖርት የባለድርሻ አካላት የውይይት መድረክ በጅማ ከተማ ሴንትራል ሆቴል እየተካሄደ ነው።

በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ የክቡር ሚኒስትሩ አማካሪ ክቡር አቶ ሞቱማ መቃሳ የኦሞ-ጊቤ ወንዝ 79,000 ስኩዌር ኪሎ ሜትር ስፋት ያለውና 7.2 በመቶ ሽፋን የሚሰጠው ስለሆነ የሃገሪቱ ትልቅ ሃብት ነው በማለት ያብራሩ ሲሆን ወንዙ ወደ ቱርካና ሃይቅ የሚፈስ በመሆኑ ኢትዮጵያም ለዚሁ ሃይቅ ሰፊ ድርሻ እንዳላት አብራርተዋል።

ክቡር አቶ ሞቱማ አክለውም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እንደሃገር የተቀናጀ የውሃ ሃብት አስተዳደር በማቋቋም በኒዘርላንድ መንግስትና በአውሮፓ ህብረት በሚደገፈው በብራይት ፕሮጀክት የተፋሰስ ዕቅድ በማዘጋጀት ወደ ተግባር መግባቱ ለዘርፉ የሰጠውን ትልቅ ትኩረት የሚያሳይ እንደሆና አባይ፣ አዋሽና ስምጥሸለቆ ሃይቆች የተፋሰስ ጽህፈት ቤት የተቋቋመላቸው መሆኑን አስገንዝበዋል።

የኦዲት ሪፖርቱ ለቀጣይ የውሃ ሃብት ዕቅድ አወጣጥና ዘላቂ አጠቃቀም ሰፊ ድርሻ አለው ያሉት ክቡር አቶ ሞቱማ በተፋሰሱ ስር የሚከሰቱ ግጭቶችን የሚፈታና የሃገራችንን እድገት ለማረጋገጥ ወሳኝ መሠረት የሚጥል በመሆኑ ዕቅዱ ወደተግባር እንዲገባ የሁሉንም ሚና የሚጠይቅ ስለሆነ እያንዳንዱ የበኩሉን አስተዋፅዖ እንዲያበረክት ጥሪ አቅርበዋል።

የብሄራዊ የተቀናጀ ውሃ ሃብት አስተዳደር ፕሮግራም አስተባባሪ ዶ/ር ብዙነህ አስፋው በበኩላቸው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የውሃ ሃብትን በዘመናዊና ዘላቂ በሆነ መንገድ ለማስተዳደር እንዲቻል የጋራ ዕቅድ በማዘጋጀት ላለፉት 10 ዓመታት በተለያዩ ተፋሰሶች የተለያዩ ተግባራትን ሲያከናውን መቆየቱን አስታውሰዋል።

የኦሞ ወንዝ በደቡብ ኢትዮጵያ የሚገኝ የሀገሪቱ ወንዝ ሲሆን ለሀገር ኢኮኖሚ፣ ለኃይል ማመንጫ፣ ለግብርና ኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም፣ እንዲሁም ለብዝሃ ህይወት ከፍተኛ ፋይዳ ያለው መሆኑን የገለፁት አቶ ብዙነህ የመርሃ ግብሩም ዓላማ በዚሁ አጀንዳ ዙሪያ ትኩረት አድርጎ በተዘጋጀው የኦሞ-ጊቤ የተፋሰስ ዕቅድ ከባለድርሻዎች ጋር ለመምከር በመሆኑ በሚገባ ግብዓት መስጠት እንዲችሉ አሳስበዋል።

በመድረኩ ከስራው ጋር ግንኙነት ያላቸው የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የዘርፉ ስራ አስፈጻሚዎች፣ ከመሬት ሃብት ማዕከል፣ ከክልል (ከደቡብ፣ ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ፣ ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ፣ ከኦሮሚያ) የተፋሰሱ አስተግባሪዎች፣ ከከፍተኛ የምርምር ተቋማት እንዲሁም ከዩኒቨርስቲዎች እየተሳተፉበት የሚገኙ ሲሆን መርሃ ግብሩ ከተጨማሪ የተፋሰሱ ቴክኒካል ቡድን ሪፓርት ማብራሪያዎች ጋር ለሁለት የቀናት የሚቆይ ይሆናል።

Share this Post